የባለስልጣናት የውጭ ሀገራት ጉዞ የቁጥጥር ስርዓት
የመንግስት ባለስልጣናት ከአገር ውጭ የሚያደርጉት ጉዞና መዳረሻዎች ላይ ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አቢይ አህመድ ገለፁ። ከአገር ውጭ ባላቸው የባንክ አካውንት ላይም ምርመራ እየተደረገ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒትሩ ለአዲሱ ካቢኔ በቀጣይ ጊዜያት እንዴት ውጤታማ ስራ መስራት እንደሚቻል በሰጡት ማብራሪያ ላይ አፅንኦት ከሰጡባቸው ጉዳዮች መካከል ከውጭ ጉዞ ጋር ተያይዞ እየመጣ ያለ ብክነት አንዱ ነው። በአንድ አመት ከ10 ጊዜ በላይ ውጭ አገር የሚመላለሱ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎችና ከዚያ በታች ያሉ ግለሰቦች መኖራቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል።
ብዙም አስፈላጊ ላልሆኑ ጉዳዮች ወደ ውጭ አገር የሚመላለሱና ከሚሄዱበት አገር በተጨማሪ ሌላ አገር ጎራ የሚሉት ባለስልጣናት በርካታ መሆናቸውን በመግለጽም የሚሄዱበት ምክንያትና መዳረሻቸው ላይ ጥብቅ ክትትል ማድረግ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
ከዚህም ሌላ የአገሪቱ ባለስልጣናት ውጭ አገር ያላቸው የባንክ አካውንት ላይ ጥናት እየተደረገ መሆኑንና ሲጠናቀቅም የተገኘው ውጤት ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ ገልጸዋል። ለዚህም የተለያዩ አገራት ትብብር እያደረጉ መሆኑን ነው የተናገሩት።
የውጭ ጉዞ አያስፈልግም የሚል እሳቤ እንዳይያዝ ብክነትን በሚቀንስ መልኩ አመጣጥኖ መሰማራት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል።
ኢዜአ