አየር መንገዱ በሴቶች የበረራ ቡድን ብቻ የሚመራ በረራውን ወደ ቦነስ አይረስ አደረገ
አለም አቀፍ የሴቶች ቀንን አስመልክቶ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሴት አብራሪዎችና የበረራ ቡድን የሚመራ በረራውን አድርጓል።
በረራው ወደ አርጀንቲናዋ መዲና ቦነስ አይረስ ከተማ የተደረገው።
አየር መንገዱ በሴት አብራሪዎችና የበረራ ቡድን ብቻ የተመረ በረራ ከዚህ ቀደም ማድረጉም ይታወሳል።
የበረራው መካሄድም ለአፍሪካውያን ሴቶች በተለይም በትምህርት ላይ ላሉት የሚፈልጉበት ደረጃ እንዲደርሱ ትልቅ መነሳሳት እና በጎ ተጽእኖ ይፈጥራል ነው የተባለው።
የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም በስነ ስርዓቱ ላይ እንዳሉት፥ ወደ አርጀንቲናዋ መዲና ቦነስ አይረስ የሚደረገው በረራ በይፋ ሲጀመር በሴቶች ቀን በሴቶች ብቻ መደረጉ ሁነቱን ታሪካዊ ያደርገዋል።
በተጨማሪም ሴቶች ሁሉንም ማድረግ እንደሚችሉ የምናሳይበት ሆኗል ነው ያሉ ሲሆን፥ ሴቶቹን በተለያዩ ደረጃዎች ለማብቃት እየተሰራ ያለው ስራ ውጤታማ መሆኑን ጠቁመዋል።
በረራው የሁለቱን ሀገራት የኢኮኖሚ እና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚያጠናክርም ተመላክቷል።
በኢትዮጵያ የአርጀንቲና አምባሳደር ጉስታቮ ቴወድሮ በበኩላቸው፥ የበረራው መጀመር ሃገራቱን በንግድ፣ ኢንቨስትመንት እና ባህል ያስተሳስራል ብለዋል።
በአለም የሴቶች ቀን አየር መንገዱ ባዘጋጀው ዝግጅት ላይ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባን ብራንድ አምባሳደር ሆና ተመርጣለች።
አየር መንገዱ ወደ አርጀንቲና በሳምንት አምስት ቀን በረራ ያለው ሲሆን፥ ዛሬ በሴቶች የተጀመረው ጉዞም ከአዲስ አበባ ተነስቶ ብራዚል-አርጀንቲና መዳረሻውን ያደረገ ነዉ።
በቤተልሄም ጥጋቡ