አሜሪካውያኑ ወላጆች በ30 ዓመቱ ከቤት አልወጣም ያለው ልጃቸው ላይ ክስ መስርተዋል
አሜሪካውያኑ ወላጆች እድሜው በመግፋቱ ምክንያት ከቤት እንዲወጣ የጠየቁት የ30 ዓመቱ ልጃቸው እምቢ በማለቱ ክስ መስርተውበታል ተባለ።
የኒው ዮርክ ከተማ ነዋሪ የሆኑት ክርስቲና እና ማርክ ሮቶንዶ ናቸው ሚካኤል ሮቶንዶ የተባለውን የ30 ዓመት ልጃቸውን የከሰሱት።
ወላጆቹ በልጃቸው ላይ ክስ የመሰረቱትም ለአምሰት ጊዜ ያክል ቤቱን ለቆ እንዲወጣ በደብዳቤ አሳውቀውት እምቢ ማለቱን ተከትሎ መሆኑም ታውቋል።
ወላጆቹ ስራውን ካጣ በኋላ ለ8 ዓመታት በነፃ ቤት ውጥስ የኖረው ልጃቸው ቤቱን ለቆ እንዲወጣ የጠየቁበትን የመጀመሪያ ደብዳቤ በየካቲት ወር ላይ ነው የላኩለት።
በደብዳቤውም “ቤቱን ለቀህ እንድትወጣ ወስነናል፤ ቤቱን ለቀህ ለመውጣት 14 ቀናት ብቻ ነው የምንሰጥህ፤ ተመልሰህ እዚህ መኖርም አይፈቀድልህም” ብለውታል።
ልጅ ለደብዳቤው ምላሽ አልሰጥ ሲልም ሌላ ተመሳሳይ ደብዳቤ ከ11 ቀናት በኋላ መልሰው የላኩለት ሲሆን፥ በተከታታይ በላኩለት ደብዳቤም ቤቱን ለቆ የማይወጣ ከሆነ በህግ ተገዶ እንደሚወጣ አሳውቀውት ነበር።
በመጨረሻም ወላጆቹ ከቤት ለመውጣት ፍቃደኛ ያልሆነውን ልጃቸውን ፍርድ ቤት ያቆሙት ሲሆን፥ ተከሳሽ ልጃቸውም ቤቱን ለቆ እንዲወጣ ወላጆቹ 6 ወር ሊሰጡት እንደሚገባ ጠይቋል።
ፍርድ ቤቱ በትናንትናው እለት በዋለው ችሎትም ልጅ ሚካኤል ሮቶንዶ በአስቸኳይ የቤተሰቦቹን ቤት ለቆ እንዲወጣ ሲል ውሳኔ አሳልፏል።
ምንጭ፦ www.ndtv.com