በዋሻ ውስጥ ለሁለት ሳምንታት የቆዩት 12 ታዳጊዎች እና አሰልጣኛቸው መውጣታቸው ተገለፀ
በታይላንድ ለሁለት ሳምንት በዋሻ ውስጥ የነበሩ 12 ታዳጊ እግር ኳስ ተጫዋቾች እና አሰልጣኛቸው መውጣታቸው የሀገሪቱ መንግስት አስታወቀ።
በሀገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል በጎርፍ ምክንያት ለሁለት ሳምንት በዋሻ ውስጥ የነበሩት ታዳጊዎች እና አሰልጣኙ እንደወጡና በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል።
ከሳምንት በላይ በዋሻ ውስጥ ከቆዩት አሰልጣኙን ጨምሮ አምስቱ ታዳጊዎች በዛሬው ዕለት መውጣታቸው ተረጋግጧል።
ባለፉት ሁለት ቀናት ከዋሻ የወጡት ስምንት ታዳጊዎች የደም እና ኤክስ ሬይ ምርመራ እንደተደረገላቸው የተገለፀ ሲሆን፥ ለቀጣይ ሰባት ቀናት የህክምና ክትትል እየተደረገላቸው በሆስፒታል እንደሚቆዩ ታውቋል።
ታዳጊዎች ከሳምንት በላይ በዋሻ ውስጥ አድራሻቸው ሳይታወቅ ቆይተው በቅርቡ በሃገሪቱ ልዩ የባህር ሃይል ቡድን በተደረገ አሰሳ መገኘታቸውም ይታወሳል።
ከ11 እስከ 16 አመት የእድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙት ታዳጊዎችና ምክትል አሰልጣኙ ታም ሉዋንግ የተሰኘውን ዋሻ ለመጎብኘት ነበር ከ9 ቀናት በፊት ወደ ስፍራው ያመሩት።
Share your thoughts on this post