fbpx
AMHARIC

በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የተከሰሱ 152 እስረኞች ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቤቱታ አቀረቡ

ታምሩ ጽጌ – ሪፖርተር

በተለያየ የሙስና ወንጀል ተግባር ተጠርጥረው የታሰሩና ክስ ተመሥርቶባቸው የሚገኙ 152 ግለሰቦች፣ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) የአቤቱታ ደብዳቤ ጻፉ፡፡

ተከሳሾቹ በቀጥታ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ዘርፍ በቀጠሮ ማረፊያ ቤት አስተዳደር በኩል እንዲደርስላቸው፣ ሰባት ገጽ አቤቱታ መጻፋቸውን ሪፖርተር ከምንጮች አረጋግጧል፡፡ ነገር ግን የቀጠሮ ማረፊያ ቤት አስተዳደር አቤቱታውን በቀጥታ ለማድረስ ኃላፊነት ስለሌለው፣ በተከሳሾች ደብዳቤ ላይ ውሳኔ የመስጠት ኃላፊነት የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር የፍትሕ ዳይሬክቶሬት መሆኑን በመጠቆም፣ ውሳኔ እንዲሰጥበት በዋና ሱፐር ኢንቴንደንት ጥላሁን አያሌው ፊርማ ሸኚ ደብዳቤ መላኩንም ምንጮች አረጋግጠዋል፡፡

በአቤቱታው የተካተቱት 152 ተከሳሾች አብዛኛዎቹ በ2009 ዓ.ም. በተለያዩ የሙስና ተግባራት ወንጀል ተጠርጥረው ክስ የተመሠረተባቸው ከፍተኛ የመንግሥት ተቋማት ኃላፊዎችና ሌሎችም ተከሳሾች ሳይሆኑ እንዳልቀሩ ምንጮች ግምታቸውን ተናግረዋል፡፡

በወቅቱ በአገሪቱ በተለይ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ተነስቶ በነበረው ተቃውሞና ግጭት ምክንያት የነበረውን የፖለቲካ አለመረጋጋት አቅጣጫ ለማስለወጥ፣ በእነሱ ላይ ተገቢ ያልሆነና ባልፈጸሙት ድርጊት ለእስርና ለክስ መዳረጋቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በደብዳቤያቸው ማሳወቃቸውን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

በመሆኑም የነበረውን ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባትና እነሱም የፈጸሙት የሙስና የወንጀል ድርጊት እንደሌለ በገለልተኛ አካል ተጣርቶ ከእስር እንዲፈቱ መጠየቃቸው ታውቋል፡፡

በአሁኑ ወቅት አገሪቱ የጀመረችው የሰላም፣ የልማትና የዕድገት ጉዞ አጋር ለመሆን፣ ለአገራቸውና ለሕዝባቸው ባላቸው ዕውቀትና ችሎታ እንዲያገለግሉ እንዲታደጓቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩን መጠየቃቸውንም የሪፖርተር ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

የተከሳሾቹ ደብዳቤ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ መድረስ አለመድረሱን ሪፖርተር ለማረጋገጥ ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡

Share your thoughts on this post
%d bloggers like this:
Visit Us On TwitterVisit Us On YoutubeVisit Us On Instagram