fbpx

HT

ሐበሻ ታይምስ ሚዲያ

AMHARIC

ሩሲያ ለኢትዮጵያ የኑክሌር ማዕከል የመገንባት ዕቅድ እንዳላት አስታወቀች

ሩሲያ የኑክሌር ማዕከልና በሩሲያ ሠራሽ ቴክኖሎጂ የታነፀ የምርምር ተቋም ለመገንባት ማቀዷን አስታወቀች፡፡ ሩሲያ ይህንን ዕቅዷን ያስታወቀችው ሪፖርተር ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ሰርጌ ላብሮቭ ጋር በኢሜል ባደረገው ቃለ ምልልስ ነው፡፡

ከየካቲት 29 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በኢትዮጵያ የሥራ ጉበኝት የሚያደርጉት ላብሮቭ፣ የሁለቱ አገሮች 120ኛ ዓመት የዲፕሎማሲ ግንኙነት በዓል ዓመቱን ሙሉ እንደሚከበር አስታውቀዋል፡፡ ይህንን ወሳኝ ግንኙነትንም ታዋቂ ግለሰቦችና ፖለቲከኞች የሚሳተፉበት የተለያዩ ሳይንሳዊ ኮንፈረንሶችና የባህል ኤግዚቢሽኖች በአዲስ አበባና በሞስኮ በማካሄድ ይከበራል ተብሏል፡፡

ላብሮቭ በሥራ ጉብኘታቸው ሁለቱ አገሮች በንግድ፣ በኢኮኖሚ፣ በኢንቨስትመንትና በኢነርጂ ዘርፎች ያላቸው ትብብር ተጠናክሮ በሚቀጥልበት ሁኔታ ላይ፣ ከኢትዮጵያ አቻቸው ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ጋር እንደሚወያዩ ገልጸው፣ በተለይ በኑክሌር ኃይል ላይ ኢትዮጵያን መርዳት እንደሚፈልጉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የተለያዩ የዓረብ አገሮች በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ ስለሚያደርጉት ወታደራዊ እንቅስቃሴ የተጠየቁት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ አካባቢው ከፍተኛ የጦር መሣሪያ ክምችት እየተደረገበት መሆኑ አሳሳቢ መሆኑን ሳይገልጹ አላለፉም፡፡ የአፍሪካ ቀንድ ሽብርተኝነትን ጨምሮ የባህር ላይ ውንብድና፣ ሕገወጥ የአደንዛዥ ዕፅ ዝውውርና ሌሎች ሰብዓዊ ቀውሶች ያሉበት አካባቢ በመሆኑ ወታደራዊ እንቅስቃሴ እየጨመረ መጥቷል ብለዋል፡፡

ሆኖም አገራቸው ሩሲያ ለየትኛውም ዓይነት ችግር ሰላማዊ በሆነ መንገድ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲ መፍትሔዎችን ተግባራዊ ማድረግ እንደምትመርጥ አስታውቀዋል፡፡

በተመሳሳይ በየመን ያለውን ቀውስ በቅርበት እየተከታተሉት መሆኑን ገልጸው፣ ቀውሱን ለመፍታት ሩሲያ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ውይይት እያደረገች ነው ብለዋል፡፡ በየመን ለተፈጠረው ሰብዓዊ ቀውስም አገራቸው ዕርዳታ እያደረገች መሆኑን ላብሮቭ ገልጸዋል፡፡

ሪፓርተር

Share your thoughts on this post
%d bloggers like this:
Visit Us On TwitterVisit Us On YoutubeVisit Us On Instagram